Thursday, October 15, 2009

የአውራዎች አንድነት

ጃርት የሚባል አውሬ-ግፍ ቢያበዛበቸው
ንቦቹ ወጡና- ከየመኖሪያቸው
ጥያቄ አቀረቡ- ለየአውራዎቻቸው።
ስብሰባ- ቁጭ አሉ፣
በስፋት-መከሩ።

አውራዎቻቸውን- ፊት ለፊት ቁጭ አርገው
እንዲህ ነገሩዋቸው
እንዲተባበሩ
መሪወቹ ሁሉ
አውራወች በሙሉ- በአንድነት ከሰሩ
ክፉ ጃርት አይመጣም- በዚህ በሰፈሩ።

ቃልም ተገባቡ-ከዚህ ቃል ላይወጡ፣
ለአናቢው ገበሬ-ትዕዛዝንም ሰጡ
አንተ ንብ አናቢ-ከዛሬ ጀምረህ
አሳየን ብለናል- በአንድ ቀፎ አድርገህ።

አናቢው ገበሬ- ልቡ እያመነታ
ትናንት በሚያውቀው- በለመደው ፋንታ
አንድ ቀፎ መርጦ- በጭስ አጠነና
ንቦችን በመሉ- ከአውራወቹ ጋራ
በአንድ አስቀመጣቸው
እንደጥያቄያቸው።

ያለ አፈጣጠሩ
ሆኖ ትብብሩ
እያንዳንዱ መሪ-ሰራዊቱን ይዞ
ቀፎው ባዶ ቀረ- ንብ ሁሉ ተጉዞ።

ድሮም ሆኖ አያውቅም፣
ትናንት ሆነ ዛሬም
አንድ የንብ አውራ ነው- ከሺህ ሰራዊት ጋር
ውጤትን የሚያሳይ- የሚጋግረው ማር፡፡

ዳግማዊ ዳዊት
ጥቅምት 2002
Ethio_dagmawi@yahoo.com

No comments: